Tidarfelagi.com

አንድ ጨለምኛ ግጥም፣ ለአንዲት ጨለምተኛ ሀገር

***
አንቺ ሃሳበ ብዙ፣
አንቺ ጓዘ ብዙ
አቅም የሚፈትን፣ጉልበት የሚያጣምን
ከህይወት ዋጋ ይልቅ በሞት ከሚያሳምን
ከዚህ ትግል ጉዞ የሚገላግሉ-
ልጆችሽ እያሉ
የት እንዲያደርስሽ ነው ሰርክ መባተሉ?
“ሁሉ ነፃ አይደለም፣ ውደቁ ተነሱ
ቆፍሩ አፈር ማሱ”
የሚሉ ቂሎችን ከጆሮሽ አርቂ
ለማይረባ ነገር ደጋግሞ መውደቅም፣ ውጤቱ ነፃ ነው ይህንን እወቂ!

ሕይወት ክብ አዙሪት
አልቦ እሽክርክሪት
መሆኑ ካልጠፋሽ፣
ለባዶው በባዶው ዘውትር ምን አለፋሽ?
መፍጨርጨር በባዶ
መጣጣር ለባዶ
በሆነበት ዓለም፣ በአልቦ ሲሳይ ሀገር
ሶስት ሺ አምስት ሺ ስድስት ሰባት በሚል እድሜ ቢደረደር፣
ከማጠር አይበልጥም የመርዘም ቁም ነገር
ነገሩን አልኩ እንጂ ነገሩስ ግልፅ ነው
ልክ እንደ ረጅሙ አጭሩም ባዶ ነው
ባዶውም ባዶ ነው መሳ ነው ትርጉሙ
ባዶ ’ሚመቱበት ባዶ እየተለሙ።
እናልሽ ዓለሜ፣
በምን ልረፍ በሚል እንዳይጠፋሽ ውሉ
ጭንቀትሽ ገብስ ነው ልጆችሽ እስካሉ
እኛ እንደሁ ነፃ ነን ሁሉ የሚያዞረን
መንገደኛ ነፋስ አዝሎ ’ሚዘውረን
ትንታግ ነን ወላፈን ሞት የሚማርከን
መፅሐፉም አውቆ አቤል እና ቃየል ብሎ ’ሚተርከን።
ልጆቼ ጦር ሜዳ ይሄዱ ይሆን ብለሽ በሃሳብ ስትዳክሪ
እኛ ኳስ ሜዳ ነን፣ እንግሊዝ ሃይቤሪ
እናልሽ ዓለሜ፣
ለማይረባ ኑሮ ጉልበት ከማጧመን
ሰሚ የሌለው ፀሎት ሰርክ ከመለመን
ባፋንኮሎ ብሎ መተዉ ጠቀመን!
ስጋት ምን አባቱ፣ የት አባቱ ሃሳብ
ጠላልፎ ሊጥለን ወደኛ የሚሳብ
ለዚህ ከንቱ ዓለም ለምን ትለፊብን ለምንስ እንልፋ፣
ለምን ከፍ ዝቁ፣ ለምን ቀና ደፋ?
የትም በማያደርስ ምንም ጎዳና ላይ ሲጓዙ ከማደር
ከቁርጥ የተቀዳ ውሳኔ መበደር
ውሳኔ!….
የነብስ ውጪ ግቢ ትግል ሳይጎትተን
ከሞት መምጣት በፊት እንተርፋለን ሞተን።

8 Comments

  • Anonymous commented on November 12, 2016 Reply

    ግሩም ነው

  • value commented on November 21, 2016 Reply

    ግጥሙ አሪፍ ነው በተለይ ደግሞ ስለ ኢትዮ ታሪክን የሚገልፅ ግጥም ቢኖር የተሻለ ነው

  • መልኬ commented on March 31, 2017 Reply

    ግጥሙን ወድጀዋለሁ

  • value commented on April 22, 2017 Reply

    Nice

  • abraham commented on April 28, 2017 Reply

    asegid tnk u…enwodihalen

  • ትእግስት commented on October 5, 2017 Reply

    በጣም አሪፍነው

  • Adisu commented on July 15, 2021 Reply

    በጣም ደስይላል

  • ናአትናይል commented on November 24, 2022 Reply

    ሀሪፍ ነው በርታልኝ

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *