በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያዎቹ ሚኒስትሮች ፲፱፻ (1900)
በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ለመጀመርያ ጊዜ ሚኒስትሮች የተሾሙት በጥቅምት ፲፬ (14) ቀን ፲፱፻ (1900) ዓ/ም ነው። በዚያን ጊዜም በዳግማዊ አጤ ምኒልክ የተሾሙት የመጀመርያዎቹ ሰባት ሚኒስትሮች የሚከተለት ናቸው።
፩ኛ/ አፈንጉስ ነሲቡ መስቀሉ — የዳኝነት ሚኒስትር
፪ኛ/ ፊታውራሪ ሃብተጊዮርጊስ — የጦር ሚኒስትር
፫ኛ/ ፀሃፌ ትእዛዝ ገብረስላሴ ወልደአረጋይ — የፅህፈት ሚኒስትር
፬ኛ/ በጅሮንድ ሙሉጌታ — የገንዘብ እና የጏዳ ሚኒስትር
፭ኛ/ ሊቀ መኯስ ከተማ — ያገር ግዛት ሚኒስትር
፮ኛ/ ነጋድራስ ሃይለጊዮርጊስ — የንግድ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር
፯ኛ/ ከንቲባ ወልደፃዲቅ ጎሹ — የእርሻና የመስሪያ ሚኒስትር
ዓጼ ምኒልክ እነኚህን ሚኒስትሮች እንደሾሙ በአዲስ አበባ ያሉ የውጭ አገር መንግስታት ተወካዮች ሹመቱን እንዲያውቁት የሚከተለውን ደብዳቤ ፃፉ።
“… የዩሮፓን ስርዓት በአገራችን በኢትዮጵያ ካሰብን ብዙ ጊዜ ነው። እናንተም የሮፓ ስርዓት በኢትዮጵያ ቢለመድ መልካም ነው እያላችሁ ስታመለክቱኝ ነበር። አሁንም የእግዚአብሄር ፍቃዱ ሆኖ ለመፈፀም ቢያበቃኝ ሚኒስትሮች ለመሾም ዠምሬ አፈንጉስ ነሲቡን፣ ፊታውራሪ አብተጊዮርጊስን፣ ፀሃፌ ትእዛዝ ገብረስላሴን፣ በጅሮንድ ሙሉጌታን፣ ሊቀመኯስ ከተማን፣ ነጋድራስ ሃይለጊዮርጊስን፣ ከንቲባ ወልደፃዲቅን አድርጌአለሁና ይህንን እንድታውቁት ብዬ ነው።”
ትቅምት ፲፬ (14) ቀን ፲፱፻ (1900) አመተ ምህረት አዲስ አበባ ተፃፈ።
ምንጭ: አጤ ምኒልክ በጳውሎስ ኞኞ